የኤማሁስ መንገደኞች

የሁለት ሰዎች ወግ እንመልከት

1. ለመሆኑ እነዚህ ሁለት መንገደኞች እነማን ናቸው?
2. የሚነጋገሩት ርዕሰ ጉዳይስ ምን ነበር?
3. በመካከላቸው ተገኝቶ የሚያስተምራቸውስ ማን ነው?
4. ለመሆኑ በቤተክርስቲያን ጉባዔያት “ሁለትም ሶስትም ሁናችሁ በስሜ ብትሰባሰቡ እኔ በመካከላችሁ እገኛለሁ” ሲባል ከልምድ ወይስ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ይዘት አለው?

እነዚህን ጥያቄዎች ከጽሑፉ ውስጥ መልሳቸውን ታገኛላችሁ መልካም ንባብ።

የኤሜሁስ መንገደኞች

ከኢየሩሳሌም ስድሳ ምእራፍ የሚርቀው ወደ ኤማሁስ መንደር ጸጥ ባለው አሸዋማ በረሃ ረጅሙን መንገድ ተያይዘውታል። የበረሃው ወበቅ ሲያዩት ወደላይ እየተምዘገዘገ ውልብ ውልብ እያለ ሲወጣ ይታያል። ሁለት ሰዎች ከመነሻቸው ጀምሮ እስከ አሁን የመጡበትን ርቀት ባለማስተዋል የልባቸውን ጭንቀት ያወጋሉ። የሚያወሩትም ስለሰሞኑ በምድረ ኢየሩሳሌም ተደርጎ የማያውቅ ወደ ፊትም የማይደረግ ግፍ ተፈጽሟል፣ ፍርድ ተስተጓጉሏል ፣ ድሀ ተበድሏል እያሉ ነበር።

ሰዎቹ የጸሐዩን ግለት፣ የመንገዱን ርቀት፣ ረሃብና ድካሙን ረስተው ስለዚያ በግፍ ስለተገደለው ደግ ሰው ያወራሉ። አብሯቸው በቆየባቸው ሦስት አመታት ውስጥ ያዩትን የተለየ ፍቅር፣ ቸርነት፣ ትህትና፣ ደግነት፣ ተዓምራት እያሰቡ፡ ከአንደበቱ እንደ ማር እያዘነበ ያስተማራቸውን የጣፈጠ ቃል እያውጠነጠኑ ይነጋገራሉ። ፍቅሩ እንደ ልክፍት ተጠናውቷቸው ስለ እርሱ ከማሰብ አልቦዘኑም። ስድሳውን ምዕራፍ እንደተጓዙ ያላስተዋሉት ሦስተኛ ሰው ተቀላቀላቸው።

ይህ ሦስተኛው ሰው ድንገትም፦ “እንዲህ እየጠወለጋችሁ ስትሄዱ እርስ በርስ የምትነጋገሯቸው እነዚህ ነገሮች ምንድር ናቸው?”ሲል ጠየቃቸው። በንግግሩ እጅጉን ተገርመው ከሁለቱ አንዱ ቀለዮጳ ፈጠን በማለት፦ “አንተ በኢየሩሳሌም እንግዳ ሆነህ ለብቻህ ትኖራለህን? በእነዚህ ቀኖች በዚያ የሆነውን ነገር አታውቅምን?” ብሎ ጠየቀው። ሰውየውም ምንም እንዳልሰማ በመሆን፦ “ይህ ነገር ምንድር ነው?” አላቸው። “ከወዴት ሀገር የመጣ እንግዳ ይሆን?” ሲሉ አሰቡና
እንዲህ አሉት፦ “በእግዚአብሔርና በሕዝቡ ሁሉ ፊት በሥራና በቃል ብርቱ ነቢይ ስለ ነበረው ስለ ናዝሬቱ ስለ ኢየሱስ፤ እርሱንም የካህናት አለቆችና መኳንንቶቻችን ለሞት ፍርድ እንዴት አሳልፈው እንደ ሰጡትና እንደ ሰቀሉት” አንድ በአንድ ከልባቸው በማዘን አወሩለት። ንግግራቸው ቀጠሉና “እኛ ግን እስራኤልን እንዲቤዥ ያለው እርሱ እንደ ሆነ ተስፋ አድርገን ነበር፤ ደግሞም ከዚህ ሁሉ ጋር ይህ ከሆነ ዛሬ ሦስተኛው ቀን ነው።” አስቀድሞ እንደሚነሳ የነገራቸው ቢሆንም አሁን ግን ሞቶ ከተቀበረ ሦስት ቀን እንደሞላው ነገሩት። ይህም ሰው ንግግራቸው በጽሞና ያደምጣቸዋል።

በእስራኤል ሁሉ የሞቱ ወሬ ተናፍሶ እነርሱም ተስፋ ቆርጠው ወደ መንደራቸው ኤማሁስ እየተጓዙ ነው። ግን ደግሞ የዛሬው የሴቶቹ ወሬ አጠራጥሯቸዋል። ቀጠል አድርገውም አሁን ደግሞ ያስገረመን አሉ፦ “ከእኛ መካከል ማልደው ከመቃብሩ ዘንድ የሄዱ ሴቶች ሥጋውን ባጡት ጊዜ ተነስቷል በዚያ የለም አሉን” አሉ ግራ በተጋባ በሰከነ ድምጽ።
ደግሞም ሴቶቹ ሥጋውንም ባጡ ጊዜ፦ “ሕያው ነው እርሱ ተነሥቶአል የሚል የመላእክትን ራእይ ደግሞ አየን” ሲሉ መጥተው ነግረውን ነበር አሉት። “ከእኛም ጋር ከነበሩት እነ ጴጥሮስ ወደ መቃብር ፈጥነው ሄደው ሴቶቹ እንደ ተናገሩት አጥተውታል፥ እርሱን ከመቃብር አላዩትም።” አሉት ድካም በተላበሰ አንደበት።

የልባቸውን መዛል የተመለከው በጸጥታ ታሪኩን ያዳምጥ የነበረው ሰው፦” እናንተ የማታስተውሉ፥ ነብያትም የተናገሩትንም ሁሉ ልባችሁ ከማመን የዘገየ፡ ክርስቶስ ይህን መከራ ይቀበል ዘንድና ወደ ክብሩ ይገባ ዘንድ ይገባው የለምን?” አላቸው።

ከሙሴና ከነብያት ጀምሮ ስለ እርሱ በመጽሐፍ የተነገረውን እየተረጎመላቸው ሲጓዙ ማምሻውን ከመንደራቸው ኤማሁስ ደረሱ። ማንነቱን ያልተረዱት በቃሉ ብርታት የተማረኩት የሩቅ ተጓዥ መንገደኛ ስለመሰላቸው አብሯቸው ያድር ዘንድ ግድ አሉት። “ማታ ቀርቧልና፡ ቀኑም ሊመሽ ጀምሯልና እባክህ ከእኛ ጋር እደር?” አሉት በሚማጽን ንግግር። እሱም ቃላቸውን ተቀብሎ ከቤታቸው ገባና አብሯቸው በማዕድ ተቀመጠ። እንጀራንም በርኮ ሰጣቸው። ተከፍተው የማያዩ አይኖቻቸው ተከፈቱ፤ እሱን አዩት፤ ያውቁታል። ረጅሙን መንገድ አብሯቸው የተጓዘው፣ ንግግሩ ልባቸውን ያቀልጠው የነበረው፣ ከሞት የተነሳው እርሱ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነው። እርሱም ከእነርሱ ተሰወረ። እነዚህ ሁለቱ መንገደኞች ሉቃስና ቀለዮጳ በደስታ ሰከሩ። ጊዜ ሳያባክኑ በፍጥነት ወደ መጡበት ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው ሮጡ፤ አሥራ አንዱ ሐዋርያትና ከእነርሱ ጋር የነበሩ ሰዎችም በአንድ ቤት ውስጥ ተሰብስበው አገኛቸው።

ሉቃስና ቀለዮጳ በመንገድ የሆነውን እንጀራውንም በቆረሰ ጊዜ እንዴት እንደ ታወቀላቸው ተረኩላቸው። “ተነስቷል! ተነስቷል! ጌታ በእውነት ተነስቷል” በደስታ ሲቃ ምስራቹን አበሰሯቸው። በመንገድ የተናገራቸውን፣ እንጀራም ሲሰጣቸው የሆነውን እየነገሯቸው ባሉበት ሰዓት በብርሃን ጸዳል የተሞላ ድምጹ የሚያሳርፍ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ በመካከላቸው ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡ ምትሃት ያዩ መንፈስም ያዩም መስሏቸው ፈሩ ደነገጡም፤ በእርግጥ ይህ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።
እርሱም፦ “ስለ ምን ትደነግጣላችሁ? ስለ ምንስ አሳብ በልባችሁ ይነሣል? እኔ ነኝ አትፍሩ አትደንግጡም፤ በእኔ እንደምታዩት፥ መንፈስ ሥጋና አጥንት የለውምና እኔ እንደሆንኩ ታምኑ ዘንድ እጆቼንና እግሮቼን እዩ ዳስሱም” በማለት አረጋጋቸው። ይህንም ብሎ እጆቹንና እግሮቹን አሳያቸው።

የዓለም ቤዛ የሆነው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አዩት፥ ተነስቷል! ደስታቸው እጥፍ ሆኖ በአይናቸው ያዩትን ማመን ቸገራቸው። ልባቸውን ያወቀው አምላክ፡ እምነታቸው ሙሉ እንዳልሆነ ተመልክቶ “በዚህ አንዳች የሚበላ አላችሁን?” አላቸው። የተጠበሰ ዓሣ ቁራጭና የማር ወለላ አቀረቡለት፤ እምነታቸው ይሞላ ዘንድ ዛሬም እንደቀድሞው በመሃከላቸው ተመገበ። አብሯቸው ሳለ በሙሴ ህግና በመዝሙራት መጻህፍት መከራን እንዲቀበልና እንዲነሳ የተጻፈው ይፈጸም ዘንድ እንደሚገባው ያስተማራቸውን ያስታውሳቸው ጀመር…
“ከእናንተ ጋር ሳለሁ በሙሴ ሕግና በነቢያት በመዝሙራትም ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ ይፈጸም ዘንድ ይገባል ብዬ የነገርኋችሁ ቃሌ ይህ ነው” አላቸው። በዚያን ጊዜም መጻሕፍትን ያስተውሉ ዘንድ አእምሮአቸውን ከፈተላቸው፤ እንዲህም አላቸው፦ “ክርስቶስ መከራ ይቀበላል በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ይነሣል፥ በስሙም ንስሐና የኃጢአት ስርየት ከኢየሩሳሌም ጀምሮ በአሕዛብ ሁሉ ይሰበካል ተብሎ እንዲሁ ተጽፎአል። እናንተም ለዚህ ምስክሮች ናችሁ።” አላቸው።

“ሰላም ለእናንተ ይሁን” ሉቃ 24:36.

ከዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ምንድን ተማርን??

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር